አየለ በየነ ፍርድ ቤት መቅረብ በነበረበት ቀን ሬሳው ለቤተሰቦቹ ቀረበላቸው /በማህሌት ፋንታሁን/

አየለ በየነ ፍርድ ቤት መቅረብ በነበረበት ቀን ሬሳው ለቤተሰቦቹ ቀረበላቸው /በማህሌት ፋንታሁን/

አየለ በየነ ዛሬ ፍርድ ቤት ቀጠሮ ነበረው። ፍርድ ቤት መቅረብ በነበረበት ቀን ነው ሬሳው ለቤተሰቦቹ የቀረበላቸው። /በማህሌት ፋንታሁን/

የ29 አመቱ አየለ በየነ በግንቦት 3ቀን 2009 ላይ ከማእከላዊ ቀርቦ ከሌሎች ሰባት ተከሳሾች ጋር የቀረበባቸው ክስ ሲነበብ በችሎት ነበርኩ። ለ9ወር ማእከላዊ ጨለማ ክፍል መቀመጣቸውን፤ ድብደባ እየተፈፀመባቸው እና ከቤተሰብ መገናኘት ሳይፈቀድላቸው መቆየታቸውን ለፍ/ቤት ተናግረው ነበር። በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ የወረዳ 10 ስራ አስፈፃሚ የነበረው አየለ በየነ መንግስት የሚያስተላልፋቸውን መመርያዎች፣ በስብሰባ የሚተላለፉት ውሳኔዎችና የፀጥታ ሁኔታዎችን ለኦነግ አመራሮች በኢሜል ያስተላልፍ ነበር በሚል የፀረ ሽብር ህጉን አንቀፅ 7(1)ን ተላልፈሃል ተብሎ ነው ክስ የተመሰረተበት።

ዛሬ ፍርድ ቤት ቀጠሮ ነበራቸው። ማረሚያ ቤቱ በምን ምክንያት እንደሞተ ሳይገልፅ መሞቱን ብቻ ለፍርድ ቤት ተናግረዋል። ፍርድ ቤቱም በቀጣይ ቀጠሮ መሞቱን የሚያረጋግጥ ማስረጃ እና በምን ምክንያት እንደሞተ እንዲያስረዱ አዟል።

በመዝገቡ 4ኛ ተከሳሽ የሆነው ይማም መሃመድ አስተያየቱን ተናግሯል።

“ማእከላዊ ህጉ ከሚያዘው ውጪ ዘጠኝ ወር ቆይተናል። የተቀጠፈው ጓደኛችን ሞተ ማለት ይከብደኛል ለአስር ቀን ምግብ አልበላም። በአስር ቀን ውስጥ በቀን ሶስት ጊዜ ህክምና እንዲሰጠው ሪፖርት ብናደርግም ምላሽ አላገኘንም። በመጨረሻ ሲደክም ሃኪም ቤት ቢወሰድም ተገቢውን ህክምና ሳያገኝ ብዙ ቆይቷል። የሞተበትን ምክንያት እንዲነገረን ከሃኪም ቤት ብንጠይቅም አልተነገረንም። የሚረዳው ቤተሰብ፣ ዘመድ እና ወዳጆች ሳያጣ መቀጠፉ ያሳዝናል። ማነው ተጠያቂው? መንግስት ከሆነ አውቀነው እንሙት።”

አንደኛ ተከሳሽ መልካሙ ክንፉም የሚከተለውን ብሏል።

“ሁላችንም ታመናል። ታምሜ ህክምና አላገኘሁም። ማእከላዊ እያለሁ የምወስደው መድሃኒት ነበረ ተቋርጦብኛል። ማመልከቻ ባስገባም ምላሽ አላገኘሁም። የአየለ ክስ እስከመጨረሻ እንዲሄድ እንፈልጋለን። ልጁ ንፁህ ነው። ምስክሮችም ይመስክሩ። ክሱ እንዲቋረጥ አንፈልግም። አውቀው ነው የገደሉት። እኛንም ይገድሉናል። ዋስትና የለንም።”

በተመሳሳይ መዝገብ ተከሳሽ የሆነውን የአየለ ወንድም (ቦንሳ በየነ) ን ጨምሮ ቀሪዎቹ ተከሳሾች እንዲሁም ቤተሰቦቻቸው በችሎት ውስጥ ሲያለቅሱ ነበር። በጣም አሳዛኝ ድባብ ነበር።

ምን እንደምል አላውቅም። የእጃቸውን ይስጣቸው!

LEAVE A REPLY