ኢትዮጵያ ነገ ዜና፡- ከትናንት በስቲያ ጉዳት ደርሶበት የተበጠሰው የባህር ዳር – ደብረታቦር – ንፋስ መውጫ – ጋሸና አላማጣ ባለ 230 ኪሎ ቮልት የከፍተኛ ኃይል ማስተላለፊያ መስመር መጠገኑን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አስታወቀ፡፡
በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የማስተላለፊያ መስመሮችና ማከፋፈያ ጣቢያዎች ኦፕሬሽን ዘርፍ የሰሜን ምዕራብ ሪጅን የኦፕሬሽንና ጥገና መምሪያ ዳይሬክተር ውበት አቤ እንዳስታወቁት ዛሬ ከማለዳ ጀምሮ በተከናወነው የጥገና ሥራ የተበጠሰውን መስመር መልሶ የማገናኘቱ ሥራ ማምሻውን ተጠናቋል።
ይህን ተከትሎም ባሕርዳር፣ ጎንደር፣ መቀሌ እና ሌሎች ከተሞች ዳግም ኃይል አግኝተዋል ማለታቸውን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል መረጃ አመላክቷል፡፡
እንዲሁም ወልዲያ፣ ኮምቦልቻና በአካባቢው ያሉ ከተሞችን ጨምሮ በኮምቦልቻ በኩል ኃይል ሲያገኙ የነበሩ ሠመራ እና ሌሎች የአፋር ክልል ከተሞች ኃይል እንዲያገኙ ለማስቻል ርብርብ እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡
በጥገና ሥራው ላይ ለተሳተፉ የሪጅኑ ባለሙያዎችና ትብብር ላደረጉ ኣካላት ምስጋና አቅርበዋል።