ህዝባዊ ትግል መቀጠሉ ነው ዋስትናው /ከአንተነህ መርዕድ /

ህዝባዊ ትግል መቀጠሉ ነው ዋስትናው /ከአንተነህ መርዕድ /

(ሚያዝያ 2018 ዓ ም)
የተደራጀ ኃይል ወደተሻለ ዴሞክራሲያዊ ስርዓስት ያደርሰኛል ብሎ ብዙ የጠበቀውና መስዋዕት ሲከፍል የኖረው የኢትዮጵያ ህዝብ ዛሬ በራሱ አመፅ የትግሉ ባለቤት ሆኗል። በኦሮምያ፣ በአማራ፣ በደቡብና በተለያዩ ቦታዎች በአምባገነኖች ጥይት ግንባራቸው እየተመታ የወደቁት፣ በእስር የሚማቅቁት፣ ተፈናቅለው የተሰደዱት ሁሉ የዚህ ወይንም የዚያ ድርጅት አባላት አይደሉም።

በተቃውሞ ሰልፍ፣ በመንገድ መዝጋት፣ ቤት ውስጥ በመቀመጥ፣ የነዳጅ ትራንስፖርት በማገድ፣ ሱቅ በመዝጋት፣ ግብር ባለመክፈል፣ ትጥቅ ላለመፍታት ገድሎ በመሞት፣ በኳስ ሜዳዎችና በህዝባዊ ስብሰባዎች ዘራፊ አምባገነኖችን በማጋለጥ፣ በመደበኛና በሶሻል ሚድያ ቅስቀሳ በማድረግ ስርዓቱን የሚይዘውና የሚጨብጠው ያሳጣው በዚህ ወይንም በዚያ ድርጅት አመራር የሚንቀሳቀስ አካል ብቻ አይደለም። የዘመናት ብሶት ያደቀቀው በቃኝ ብሎ ለተመሳሳይ ዓላማ የተነሳ መላው የኢትዮጵያ ህዝብ ነው። ይህን ስል የተደራጁ የተቃውሞ ኃይላትን አስተዋፆ ለማቃለል ሳይሆን አሁን በኢትዮጵያ የሚካሄደው ህዝባዊ አመፅ ዋናው ባለቤቱ ህዝቡ መሆኑን ለማመልከት ነው።

ቲም ለማ፣ ቲም ገዱ ወዘተ.. ከህወሃት ጉያ ወጥተው የነገዋን ብሩህ ኢትዮጵያ ለመገንባት የትግሉ አካል እንዲሆኑ መንገድ የጠረገላቸውና ያስገደዳቸው ህዝባዊ አመፁ ነው። በተፈጥሯቸው ለዴሞክራሲያዊ ለውጥ መስዋዕት ለመክፈል ከመጀመሪያው ከህዝብ ጎን የተሰለፉ ሳይሆኑ በህወሃት አገልጋይነት ተኮትኩተው ያደጉ መሆናቸው ሊዘነገጋ አይገባም። ህዝባዊ ትግሉ የቀዘቀዘና የህወሃት ጉልበት የበረታ ከመሰላቸው ወደ ቀድሞው የአገልጋይነት ባህሪያቸው ሊመለሱ ይችላሉ። እንደ እስክንድር ነጋ፣ በቀለ ገርባ፣ አንዷለም አራጌ፣ ተመስገን ደሳለኝ ለህዝባዊ ትግሉ ህይወቴን እሰጣለሁ ብሎ የመድፈር የቆረጠ ውስጣዊ ባህርይ ከነሱ ከጠበቅን የዋህ ነን። እንደ እርሾ ውስጣቸው ያለችውን ጥፍጣፊ ህዝባዊ ባህሪ ኮትኩቶ ያሳደገላቸው ውጫዊው ህዝባዊ አመፅ ነው። ህዝባዊ ትግሉ ከበረታ ሊበቀላቸው ከማይመለስና ከሚያውቁት ጨካኝ አሳዳሪያቸው ህወሃት ይልቅ በበጎ ዐይኑ እያየ ከሚያደንቃቸውና አይዟችሁ ከሚላቸው ህዝብ ጎን ይቆማሉ። እነሱን የሚያንቀሳቅሰው ሞተር ተገቢውን ሃይል የሚያገኘው ከህዝባዊ ትግሉ ነው። ህዝባዊ ትግሉ ከደከመ በፍጥነት እንደሚጠወልጉ ልብ ልንል ያስፈልጋል።

ዶክተር አብይ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ከተረከበ በኋላ ባደረገው ንግግር ላለፉት አርባ ዓመታት ያልሰማናቸውን ኢትዮጵያን፣ ህዝቧንና አንድነቷን ያወደሰ ቁም ነገር ላይ አተኩሯል። ንግግሩ ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን ያስደመመ ነበር። በእውቀት ላይ የተመሰረተ ትሁትና ታሪካዊ ንግግር የሚያስመሰግነው ቢሆንም ይህንን መድረክ ያመቻቸለት ህወሃት መስማት የማይፈልገውን እንዲጋት ያስገደደው ህዝብ አሁንም አብይን የተናገረውንና ሌላውንም ጠቃሚ ነገር እንዲሰራ የሚያስችለው ይኸው የኢትዮጵያ ህዝብ ነው። አብይንና ጓደኞቹን ወደፊት ገፍቶ ያስገባው ህዝብ ሥራውን ጀመረ እንጂ አላጠናቀቀም። ቄሮ፣ ፋኖ፣ ዘርማ፣ የጎበዝ አለቃና ሌላውም ኢትዮጵያዊ ወያኔዎቹ ትግሉን እንዳይቀለብሱት ነቅቶ መጠበቅና በስልት እያስገደደ ወደፊት መራመድ አለበት። ህዝቡ ባያስገድዳቸው ኖሮ ህወሃቶች በጠቅላይ ሚኒስትር ቦታ አብይን ማየት አይፈልጉም ነበር።

የህወሃት ዘራፊ ኃይሎች ህዝባዊ ትግሉ እጃቸውን እየጠመዘዘ ድሉን መውሰድ ካልጀመረ በነፃ የሚያስረክቡበት ማበረታቻ (incentive) የላቸውም። ትግሉ ደከም ያለ ከመሰላቸው ተገደው የሰጡትን መልሰው እንደሚወስዱ የእነአንዱዓለም ተመልሶ መታሰር ጉልህ ማስረጃ ነው። ብዙ ኢትዮጵያውያን ዶ/ር አብይ ምን ማድረግ እንዳለበት የሥራ ዝርዝር (prescription) በመስጠትና በንግግሩ በመማለል ላይ ተጠምደዋል። ህወሃት በበኩሉ ደግሞ ይህንን ህዝባዊ አመፅ አስቁሞ ህልውናውን ለመጠበቅ ተንኮል በመሸረብና በማድባት ላይ ነው። መቀሌና አዲስ አበባ በር ተዘግቶ ሌት ተቀን የሚመከረው ይኸው መሆኑን የማይገነዘብ የዋህ በሞላባት ኢትዮጵያ ትግሉ መራራ ነው የሚሆነው።

የዴሞክራሲያዊ ኃይላት ከትናንት ይልቅ ዛሬ በጣም ወሳኝ ወቅት ላይ መሆናቸውን ተገንዝበው እጥፍ ድርብ የሚሠሩበት ወቅት ላይ እያሉ በባዶ ተስፋና በብልጭልጭ ውጤት ላይ ማተኮሩን አቁመው፤ የተገኙ ድሎችን ለማስጠበቅና ወደተሻለ ድል ለመገስገስ ህዝባዊ ትግሉን ማጠናከር ላይ መረባረብ አለባቸው።

ሥርዓቱ ተገድዶ የህዝቡን ጥያቄዎች እንዲመልስ ለጠቅላይ ሚኒስትር አብይና ባልደረቦቹ ጠንክሮ መውጣት ዋስትናው የህዝቡ ትግልነው። ህወሃት ጦሩን ተጠቅሞ ህዝብ ከመግደልና ከማስፈራራት እንደማይመለስ ደጋግሞ አሳይቷል። ደህንነቱ ሙሉ በሙሉ በመንደር ልጆች የተያዘ ነው። ከዚያም በላይ አስቸኳይ አዋጁ አብይን ምንም እንዳይሠራ ያደርገዋል። ህወሃቶች አብይን ቤተመንግሥት ውስጥ የታሰረ እቃ ከማድረግ የማይመለሱ ስለሆነ ህዝባዊ ትግሉ በተናበበ ሁኔታ መቀጠል አምባገነኖችን ፋታ ይነሳቸዋል፤ ህዝቡንም የድሉ ፍሬ ባለቤት ያደርገዋል።

በሰላማዊ የህዝብ ትግል ላይ ተመራማሪ የሆነው ጂን ሻርፕ “Resistance, not negotiations, is essential for change in conflicts where fundamental issues are at stake. In nearly all cases, resistance must continue to drive dictators out of power. Success is most often determined not by negotiating a settlement but through the wise use of the most appropriate and powerful means of resistance available” በተቀራራቢ ለመተርጎም “መሰረታዊ የህዝብ ጥያቄዎች ባልተመለሱበት ሁኔታ ለለውጥ ወሳኙ ህዝባዊ መከላከል እንጂ ድርድር አይደለም። አምባገነኖችን ከስልጣናቸው ለማስወገድ ህዝባዊ አመፅ መቀጠል ያስፈልጋል። ድል የሚረጋገጠው በድርድር ሳይሆን ያለውን ሃያል ህዝባዊ አመፅ ስርዓት ባለው መልክ በመጠቀም ነው” ይላል። ስለሆነም ቄሮ፣ ፋኖ፣ የጎበዝ አለቆች፣ ዘርማ ወዘቱ.. የጀመሩት ትግል የበለጠ እየተጠናከረና እየተቀናጀ መቀጠሉ ነው ድሉን የሚያቀርበው።

አሁን ከጫጫታውና ከስሜታዊነት ወጥተን ህዝቡ በሰከነ ሁኔታ ትግሉን እንዲቀጥልና የተገኘውንም ድል እንዲያስጠብቅ ማስቻል የሁላችንም ድርሻ ነው። ህዝቡ ትግሉን በሜዳ ብቻ ሳይሆን እየተሰዋ ቤተመንግስትና ፓርላማ ውስጥ ሳይቀር አስገብቶታል። በቅንጥብጣቢ ልዩነት እርስ በርስ በሃሳብ መራኮቱ ገትተን የህዝቡን ትግል ዳር ማድረስ አለብን። አይደለም አሁን የተሟላ ዴሞክራሲም ሰፍኖ ትግል አይቆምም። ማስጠበቁ ራሱ ትግል ነውና።

LEAVE A REPLY