በደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ በአንድ ተማሪ ሞት የተጠረጠሩ ተማሪዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸው ተገለፀ

በደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ በአንድ ተማሪ ሞት የተጠረጠሩ ተማሪዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸው ተገለፀ

ኤፍ ቢ ሲ ||  ዩኒቨርሲቲው ባወጣው መግለጫ ዓርብ ግንቦት 16/2011 ዓ.ም ከቀኑ 11 ሰዓት አካባቢ ምንጩ ያልታወቀ ጥቃት በተማሪዎች ላይ ደርሷል ብሏል።

ጥቃቱ ከተለመደው የተማሪ ፀብና ግርግር ለየት ያለ ባህሪ ያለው ሲሆን፥ ጩኸትና ግርግር የማይታይበት ተማሪዎችን በአሰቃቂ ሁኔታ ጥቃት የሚያደርስ ነበርም ነው ያለው።

ጥቃት አድራሾችም ፊታቸውን በመሸፈናቸው በቀላሉ ለመለየት አስቸጋሪ ነበር ያለው ዩኒቨርሲቲው፥ ሆኖም ግን አርብ ጥቃቱን ካደረሱ በኋላ ከግቢ ወጥተው ወደ ጫካ ሲገቡ በማህበረሰቡ ጥቆማ የተወሰኑትን የፀጥታ ሃይሎች በቁጥጥር ሥር አውሏቸው ምርመራ እየተደረገባቸው እንደሚገኝ ተጠቁሟል።

የደብረ ማርቆስ ከተማ ነዋሪዎች ስለ ችግሩ እና ስለ ቀጣይ የተማሪዎች ሰላም ተወያይተዋል።

ድርጊቱን ያወገዙት ተወያዮቹ ችግር ፈጣሪዎቹን በማጋለጥ ለፀጥታ አካላት እንደሚሰጡም ቃል ገብተዋል።

እስካሁን በድርጊቱ የተጠረጠሩ ተማሪዎችም በቁጥጥር ስር መዋላቸውም ነው በውይይቱ ላይ የተገለፀው።

የአማራ ክልል የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤትም የክልሉ መንግሥት እና ሕዝብ በደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ በአንድ ተመራቂ ተማሪ ላይ በደረሰዉ የሕይወት መጥፋት ከልብ ማዘኑን በመግለፅ ድርጊቱን አጥብቀው እንደሚያወግዙት ገልጿል።

የክልሉ መንግሥት ከሕዝቡና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመተባበር ጥቃት አድራሾችን ተከታትሎ ለሕግ እንደሚያቀርብ ማስታወቁንም ነው አብመድ የዘገበው።

የትግራይ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ባወጣው የሀዘን መግለጫም በደብረማርቆስ ዩንቨርሲቲ ተማሪ በነበረው ወጣት ሰዓረ አብርሃ ህልፈተ ህይወት የተሰማዉ ጥልቅ ሃዘን ገልጿል።

ጉዳዩን በአፅንኦት እየተከታተለው እንደሚገኝ የገለፀው የክልሉ መንግስት፥ ወንጀለኞች ወደ ህግ እንዲቀርቡ እና አስፈላጊዉ ፍርድ እንዲያገኙ ከሚመለከተዉ አካል ሆኖ እንደሚሰራ በመግለፅ ለሟች ቤተሰብ፣ ወዳጅና ዘመድ መፅናናትን ተመኝቷል።

LEAVE A REPLY