የኢትዮጵያ ፖለቲካ ከተሳከረበት ከስልሳዎቹ ጀምሮ እስከዛሬ ስካሩ አልበርድ ብሎን እንደተንገዳገድን አለን። የፖለቲካ ስካራችን ብርቱ ይሁን እንጂ አንደሃገር ወድቀን አናውቅም። ከስካር መልስ ዞሮ መግቢያችንና ማደሪያ ቤታችንን ለውጪጠላት አሳልፈን አልሸጥንም።
መከፋፈልና መበጣበጥ በቤተሰብ ውስጥ ያለ የንትርክ ወጤት ስለሆነ ውሎ አድሮ ወደ አንድነትና ሰላምመምጣቱ አይቀርም። ኢትዮጵያዊያን በውስጥ ቢከፋፈሉም የውጪ ጠላት ሲመጣባቸው አንደ አንድ ሰውቆመው፤ እንደ አንድ ልብ መክረው፤ እንደ አንድ ቤት ሆነውጠላታቸውን ሲአሳፍሩ እንጂ እጅ ሲሰጡ አይታወቅም። ችግራችን ለጠላት አጋጣሚ የፈጠረ መስሎ ቢታይም በቁርጥጊዜ ሰምና ወርቅ ሆነን በጋራ ጠላታችንን ከማጥቃትና ሉዓላዊነታቸንን ከማስከበር አላመነታንም። ይህ የሩቅና የቅርብ ታሪካችን ሕያው ምስክር ሆኖ በዓለም ሲነገር ኖሯዋል።
በጣሊያን ወረራ ጊዜ መሳፍንቱ ልዩነታቸውን ገሽሽ አርገውየፋሽስትን ታንካና አውሮፕላን በዱላ፤ በአልቪን፤ በጓንዴ፤ በምኒሽር፤ በወንጭፍ፤ በፈረስ፤ በጎራዴ አውድመው ነፃነታቸውን እና ሉዓላዊነታቸውን አስከብርዋል። እቴጌ ጠሐይቱ የውጫሌን ውል አልፈርምም ሲሉ ሕዝቡ በአንድ ድምፅ ደገፏቸዋል። ክብር ለነርሱ ይሁን።
የገበያ ግርግር ለሌባ ያመቻል እንዲሉ ሕዝባችን በነጭና በቀይሽበር ሲናወጥ፤ ሰራዊታችን ከሻቢያና ከወያኔ ጋር በውጊያመጠመዱን ያየው ሲያድ ባሬ ድሬደዋ ዘልቆ የግዛት ሉዓላዊነታችንን ተዳፍሯል። ይሁን እና የኢትዮጵያ ሕዝብ እንደአንድ ልብ መክሮ፤ እንደ አንድ ህዝብ ቆሞ ጠላቱን አዋርዷል።
የደርግ ባለሥልጣናት የሃሳብና የርዕዮተዓለም ልዩነትቢኖራቸውም በኢትዮጵያ ሉአላዊነት ላይ በአንድ ድምጽ መክረዋል። የደርግ ካዝና ነጥፎ ችግር ላይ በወደቀበት ጊዜጋዳፊ የ140 ሚሊዮን ዶላር ብድር እንደሚሰጥ ቃል ይገባል። የወቅቱ የብሔራዊ ባንክ ገዥ አቶ ታደስ ገ/ኪዳን የብድር ውልእንዲፈራረሙ ሊቢያ ይላካሉ። የተደረገላቸው እቀባበል ቀዝቃዛ ከመሆኑ ባሻገር ውሉ በአረብኛ እና በእንግሊዘኛ ተዘጋጅቶና የአረብኛው ውል ቅጂ አሳሪ (binding) እንደሚሆን ሆኖ ይጠብቃቸዋል። ታደሰም ውሉንና ስምምነቱን እንዲፈርሙ ይጠይቃሉ። የምኒሊክ ውል ትዝ ይላቸውና አልፈርምም ይላሉ። ብዙ አየሁ በተሰኘው መጽሐፋቸው ገጽ 239 “የውጫሌ ውል ትዝ አለኝ። …አጼ ምኒልክ ያተኮሩት በአማርኛው ቅጂ ውስጥ በተጻፈው ስለነበር በጣልያንኛ የተጻፈው ችግር ያመጣል በለው አላሰቡም። ዓይኔ እያየ እንዴት ዳግማዊ ውጫሌ ውል እፈርማለሁ?” አሉ።
ግራቀኙን የሚአግባባው የእንግሊዘኛው ቅጂ አሳሪ (binding) ሆኖ መፈራረም እንደሚገባ ታደሰ በአጽኖት ለአረቦች ይገልጻሉ። ለመፈረም የተቸገሩበትን ሲገልጹም ”አረበኛው የበላይነት አለው ብዬ መፈረም ያልፈለግሁበት ዋና ምክንያት ሊብያ ገንዘብ ስላላት ብቻ ድሃ ሃገሮችን ጎትታ እያመጣች ክብረ ነክ ውል አንዲፈራረሙ ማስገደዷ መንፈሴን ስላሸፈተውናውስጤ የሚንቦገቦግ ንዴት ስለ ነበረ ነው።” አልቆቻቸው ከሊብያ የሚፈለገው ገንዘብ ስለሆነ በፈለጉት ቋንቋ ፈርምና ገንዘቡን ይዘህ ተመለስ የሚል ትእዛዝ ቢሰጣቸውም ታደስያበጠው ይፈንዳ በሚል መፈራረሙን ትተው ወደ ኢትዮጵያለመመልስ ወደ ትሪፖሊ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ጣቢያ ጉዞይጀምራሉ። ብዙ ሳይቆይ ጋዳፊ የፀጥታ ሃይሉን ልኮ ታደሰን በማስመለስ የእንግሊዘኛው ቅጂ አሳሪ ውል አስደርገው በመፈራረም ገንዘባቸውን ይዘው በድል ተመልሰዋል። ይህ ነው የኢትዮጵያዊያን ወኔና ክብር።
አሁን ላይ ጋዳፊ እንዴት ተዋርደው ከስልጣን እንደተባረሩና እንደተገደሉ ሁላችንም እናውቃለን። እንደ ሃገር ሊቢያ በእርስበርስ ጦርነት እየወደመች አለች። ኢትዮጵያና ታደሰ ሉዓላዊነታቸውን እና ክብራቸውን እንደጠበቁ ይገኛሉ።
የኢትዮጵያ ሕዝብ ከወያኔ/ኢሕአዴግ ጋር ሰፊ ቀራኔናአለመግባባታ ደርሶ እንደነበር ይታወሳል። ኤርትራ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነትና አንድነት በሚፈታተን ደረጃ ወረራ ስትፈጽም ሕዝቡ ከኢሕአዴግ ጋር ያለውን ልዩነት አርግቦ በአንድነት ወደባድሜ ግንባር ዘምቷል። ወራሪውን ሃይል አሸንፎ የኢትዮጵያን አንድነት አስከብሯል። እነዚህ ክስተቶች የሚአሳያቱ ኢትዮጵያዊያን ለውጭ ሃይል አጎብድደው እንደማያውቁ፤ በዓለም አቀፍ ድርድሮችና ውሎች ሁሉ የኢትዮጵያን ጥቅም አሳልፈው ላለመስጠት ብዙ ፈተና ተቋቁመው በአሸናፊነት የተወጡ መሆኑን ነው።
በህዳሴው ግድብ ዙሪያ ኢትዮጵያዊያን የተለያዩ አቋሞች፤ አመለካከቶችና ልዩነቶች ነበሯቸው። ይህ ፀሐፊ የግድቡን መገንባት ቢደግፍም በግንባታው ቦታ አመራረጥ (project site)ላይ ልዩነትና ጥያቄ ነበረው። ለምን ከሱዳን ድንበር አርባ ኪሎሜተር እርቀት ላይ እንደተገነባ እስካሁን አጥጋቢ መልስ አላገኘም። ይሁን እና ዘግይቶ የተጀመረ ግን በጣም ጥሩ (something too good that came late) ስራ በመሆኑ ደስተኛ ነው። ብዙዎችም የተለያየ ተቃውሞና ልዩነት አላቸው። የሃገርሉዓላዊነትን እስካልተገዳደረ ድረስ ልዩነታችን ጤናማ ነው።
እንደ ኢትዮጵያ መንግስት ዘገባ 69% የሚሆነው የግድቡ ስራ በመከናወኑ ኢትዮጵያዊያን ተደስተዋል። ግብጽና ሱዳን ስላልተደሰቱ በውሃው አሞላል ዙሪያ ውዝግብ አስነስተዋል። ግብጽ ጥቅሟን ለማስጠበቅ የምታደርገው ዋይታ ስለሆነ ሊያስደንቀን አይገባም። ልንነግራት የሚገባው ጉዳይ ቢኖርእኛም ጥቅማችንን እና የተፈጥሮ ሃብታችንን የማስጠበቅ ሃላፊነትና ግዴታ እንዳለብን ነው።
ከባልሽ ባሌ ይበልጣል ከሆነ ለግብጽ የምናበድረው ውሃና ዱቄት ስለሌለን ባለችበት አሽዋዋን ትበደር። በአሜሪካ በኩልገብታ ያልተገባ ውል ልታስፈርም መሞከሯ ግን ለኢትዮጵያ ያላትን ንቀት ገላጭ ነው። በዚህ ዘመን የቅኝ ገዥዎች ውል፤ ብልጣብልጥነትና ስግብግብነት ቦታ የሌለው እንደሆነ ግብጽን በሚገባት ቋንቋ መንገር ያስፈልጋል።
ሃያሏ አሜሪካም ድህነታችንንና የውስጥ ችግራችንን ተመልክታ እጅ በመጠምዘዝ የውጫሌን ውል ለማስፈረም ካሰበች ምን ብንቀጥን የነአብዲስ አጋ፤ የነሚኒሊክ፤ የነጠሃይቱ፤ የነጃጋማኬሎ፤ የነቲወድሮስ፤ የነኡመር ሰመትር፤ የእነታደሰ ገ/ረኪዳንልጆች መሆናችን ይነገራት።
ትራምፕ እያደረገ ያለው ወራዳ የዲፕሎማሲ ጫናየፕሬዚደንቱን ታሪክ አላዋቂነት ማሳያ ነው። አንኳን በዚህ ዘመን በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ጊዜ አሜሪካ ኢትዮጵያን ከድታ ለጣሊያን ስትወግን ኢትዮጵያ አልተሸነፈችላትም። የአሜሪካ የፖሊሲ አውጭዎች ከታሪክ መማር አለመቻላቸው ግን ይገርማል። እነዚህ ፖሊሲ አውጭዎች ድንቁርናን እንደገነት (ignorance is a bliss) ቆጥረውት ይሆን።
ድህነት ያዋርዳል፤ ከሰው በታች አርጎ ያሸማቅቃል፤ በፍርሃት ያሳስታል፤ ክብር ያጎድፋል። ይህ በዓለማችን የሚታይ ክስተት ቢሆንም ድህነትና ኋላቀርነት እያዩ ማዋረድ፤ ማሸማቀቅና መዳፈር ግን ኢግብረገባዊ ነው። ሃይልን ተማምነው ድሃን ማንበርከክ ፈልገው ከሆነ ደግሞ በዓለማችን ሃያል ሃገር አሜሪካብቻ አለመሆኗን ብናሳውቃት እራሷንም ይጠቅማል። ስለሆነም አሜሪካ ከህዳሴው ግድባ ላይ እጅሽ አንሺ። ግብጽም አደብ ገዝተሽ በነፃ የሚወርድልሽን የጊዎን ፀበል ጠጪ። የጦርነት ነጋሪት ከጎሰምሽ ከካይሮ የበለጠ ነጋሪት አዲስ አበባም አለ። አያርገውና ጦርነት ብትጭሪ የሕዝብሽንና የሃገርሽን መጥፊያ ክብሪት መጫርሽን ተረድተሽ ጫሪው። ነን ሶቤ!
ቀን፣ የካቲት 23፣ 2012

























