ልዩ ጥንቅር || ኢትዮጵያ ከ5 ዓመቱ ወረራ ነፃ የወጣችበት “ሚያዝያ 27 አርበኞች...

ልዩ ጥንቅር || ኢትዮጵያ ከ5 ዓመቱ ወረራ ነፃ የወጣችበት “ሚያዝያ 27 አርበኞች ድል ቀን” በዓል! 

ኢትዮጵያ ነገ ዜና–  የዛሬ 85 ዓመት፣ ጣሊያን በአድዋ የደረሰባትን ሽንፈት ለመበቀል እና ኢትዮጵያን ቀኝ ግዛት ለመያዝ 40 ዓመታትን ስትዘጋጅ ከርማ በ1928 ዓ.ም ለመላው የጥቁር ሕዝብ እንደ ነጻነት ምልክት ተደርጋ የምትታየውን ኢትዮጵያን ወረረች፡፡

የኢትዮጵያ ሕዝብም በአንድነት የጣሊያንን ወረራ ለመከላከል ጨርቄን ማቄን ሳይል ተነሳ፡፡ በሰሜን እና በምስራቅ በተካሄዱ ጦርነቶች ግን ኢትዮጵያዊያን እንደ አድዋው ድል አልቀናቸውም፡፡ ንጉሠ ነገሥቱ በተሳተፉበት የማይጨው ጦርነትም ድል ባለመገኘቱ ኢትዮጵያዊያን የአርበኝነት ተጋድሎ እንዲጀምሩ አደረጉ፡፡

ከጣሊያን መድፍ እና የአውሮፕላን መርዝ የተረፉ ቆራጥ አርበኞች ዱር ቤቴ አሉ፡፡ እንደ እጃቸው መዳፍ ጠንቅቀው የሚያውቁትን የአገራቸውን መልክዓ-ምድር መመኪያ አድርገው ጣሊያንን ይፋለሙ ጀመር፡፡ ከመኳንንቱ እና ከመሳፍንቱ በተጨማሪ ብዙ አገር ወዳድ ኢትዮጵያዊያን የአርበኝነት ትግሉን ተቀላቀሉ፡፡

በበጌምድርና አካባቢው ራስ ውብነህ ተሰማና ቢትውደድ አዳነ፤ በጎጃም ቢትወደድ መንገሻ ጀምበሬ፣ በላይ ዘለቀ (አባ ኮስትር)፣ ደጃዝማች ኃይለየሱስ ፍላቴ እና ራስ ኃይሉ በለው፤ በሸዋ ራስ አበበ አረጋይ፣ መስፍን ስለሺ ፀሐይ ዕንቁሥላሴ፤ የበሼ ቤተሰቦች ደጃች ተሾመና የሽንቁጥ ቤተሰቦች፤ በወሎ እነ ኃይሉ ከበደ፣ ወሰን ኃይሉ እና በሌሎች የአገራችን ክፍሎች የሚገኙ አርበኞች ሕዝቡን በማስተባበር ጣሊያንን ለአምስት ዓመት የረገጣት የኢትዮጵያ ምድር ረመጥ እንድትሆንበት አደረጉ፡፡

ከአምስት ዓመት ተጋድሎ በኋላም ጣሊያን ድጋሚ የሽንፈትን ጽዋ ተጎነጨ፡፡ ታሪካዊቷ ሰንደቅ አላማም ሚያዚያ 27/1933 ዓ.ም ልክ የዛሬ 80 ዓመት ድጋሚ በኢትዮጵያ ሰማይ በነጻነት ለመውለብለብ በቃች፡፡

80ኛው ዓመት የኢትዮጵያ አርበኞች የድልና የነፃነት ቀን አራት ኪሎ በሚገኘው “ድላችን ሀውልት” በድምቀት ተከብሯል።

ጣልያን ኢትዮጵያን ዳግም ለመውረር ጥረት ባደረገበት ጊዜ ጀግኖች አባቶች እና እናቶች አይበገሬነታቸውን ያስመሰከሩበት ድል በሚታሰብበት በዛሬው የድል በአል ወጣቶች በፉከራ እና ሽለላ የአገር ተረካቢነታቸውን አስመስክረዋል፣ የማርሽ ባንድ ትርኢትም ቀርቧል።

ቀኑን በማስመልከት “የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት” ያስተላለፉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ “የኢትዮጵያ አርበኞች ቀን ጀግኖች አርበኞቻችን ሀገራችንን ከአምስት ዓመቱ የጣሊያን ወረራ ነፃ ያደረጉበት ቀን መታሰቢያ ነው። ይህን ቀን ስናስብ ከጀግኖች አርበኞቻችን ሦስት ነገሮችን እየተማርን መሆን ይገባዋል። የመጀመሪያው ከምንም ነገር በላይ ሀገርን ማስቀደም፣ ሁለተኛው ለሀገር ማንንም አለመጠበቅ እና ሦስተኛው የዜጎች አንድነት ናቸው” ብለዋል።

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ደግሞ፣ ሚያዝያ 27 የዛሬ 80 ዓመት ጀግኖች አርበኞች ኢትዮጵያን ከአምስት ዓመቱ የጣሊያን ወረራ ነፃ ያወጡበት ታላቅ ቀን መሆኑን ጠቅሶ “ይህንን የድል ቀን ስናስብ ጀግኖች አባት አርበኞች ወራሪ ጠላትን በመመከት፣ የሀገርን ዳር ድንበር በማስከበር፣ ለትውልዱ እንዳስረከቡት ሁሉ እኛም በዘመናችን ከውጪም ሆነ ከውስጥ በሀገር ላይ የሚቃጣውን የጥፋት ሐሳብ እና ድርጊት በመመከት ለመጪው ትውልድ ዳር ድንበሯ የተከበረች ሀገር ለማስረከብ እጅ ለእጅ በመያያዝ የራሳችንን ታሪክ ልንጽፍ ይገባል” ሲል ጥሪ አቅርቧል።

የአርበኞች ቀንን ምክንያት በማድረግ የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት ያስተላለፉት ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ በበኩላቸው “የጥንት ኢትዮጵያ አርበኞች አገራችን ነጻነቷን ጠብቃ እንድትኖር አድርገዋል። ዛሬም አገርን ለመጠበቅና ለመገንባት አርበኝነት ከሁላችንም ይጠበቃል፡፡ ያለፈውን ጀግንነት የምናቆየው ለዚህ ከተነሳን ነው” በማለት ተናግረዋል።

በተያያዘ፣ 80ኛው ዓመት የአርበኞች ድል ቀን በአል ዛሬ አራት ኪሎ በሚገኘው የድል ሀውልት በተከበረበት ወቅት በቦታው ተገኝተው የመታሰቢያ አበባ ያስቀመጡት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ወይዘሮ አዳነች አቤቤ፣
የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሥር በሚገኙ ሆስፒታሎች ውስጥ በነፃ የህክምና አገልግሎት እንዲያገኙ መወሰኑን ገልጸዋል።

“ውሳኔው የተላለፈው ለጀግኖች ክብር ሲባል ነው” ያሉት ምክትል ከንቲባዋ፣ ለጀግኖች አርበኞች ከተማ አስተዳደሩ መሬት ለመስጠት መወሰኑን አብስረው “የነጭ ወራሪን ሴራ በቀላሉ የተረዱ እና የዛሬው ትውልድ በአገሩ እንዲኮራ ያደረጉ አባቶች ክብር ይገባቸዋል። ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ቅኝ ያልተገዛች አገር መባሉ ትልቅ ኩራት ነው። የዛሬው ትውልድም የጀግኖች አባቶችን ወኔና ማስተዋልን መውረስ ይገባዋል” ሲሉ አሳስበዋል፡፡

የኢትዮጵያ ነገ ዝግጅት ክፍል፣ ለመላው ኢትዮጵያውያን እንኳን ለድላችንና የነፃነታችን ቀን አደረሳችሁ በማለት መልካም ምኞቱን ይገልፃል።

LEAVE A REPLY