የመንግስት መገናኛ ብዙሃን ስለ ምሩጽ ይፍጠር በድጋሚ እየዋሹ ነው

የመንግስት መገናኛ ብዙሃን ስለ ምሩጽ ይፍጠር በድጋሚ እየዋሹ ነው

ድርብ ወርቅ በማምጣት ሃገሩን ከክብር ማማ ላይ ያወጣውና በያዝነው ሳምንት ህይወቱ አልፎ በቶሮንቶ ቅድስት ማርያም ካቴድራል የፍታትና የሽኝት ስነ ስርአት የተፈጸመለትን ምሩጽ ይፍጠርን በተመለከተ የመንግስት መጋናኛ ብዙሃን በድጋሚ የውሸት ዘገባዎችን በማቅረብ ላይ ናቸው፡፡

ምሩጽ በህይወት እያለ መሞቱን የዘገበው ኢቢሲ የተባለው የመንግስት ቴሌቪዥን አሁንም በምሩጽ ጥብቅ ማሳሰቢያ የሽኝት ስነ ስርዓቱ በቅድስት ማርያም ካቴድራል መደረጉ ይፋ ሆኖ እያለ በተራ እልኽ የሚታወቀው ህወሃት መራሹ የኢህአዴግ መንግስት የመገናኛ ብዙሃን በወያኔ መንግስት ቁጥጥር ስር ባለው በቶሮንቶ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን የሽኝት ስነ ስርዓቱ መፈጸሙን በቴሌቪዥንና በራዲዮ ስርጭቱ ማሰማቱ ታውቋል፡፡ /ቪድዮውን ለማመሳከር ይመልከቱ/

በህጋዊው ሲኖዶስ ስር በምትተዳደረው ቅድስት ማርያም ካቴድራል ሃዘን መድረስ እንደሚፈልጉ በካናዳ የኢትዮጵያ አምባሳደር ወ/ሮ ብርቱካን አያኖ ጠይቀው ምንም አይነት ተቃውሞ እንዳይነሳና የኦሎምፒክ ጀግናውን አስከሬን ለመሸኘት ማንም ሰው ቢመጣ በኢትዮጵያዊ ጨዋነት ተስተናግደው እንዲሄዱ መደረጉ የሚታወስ ሲሆን ቴሌቪዥኑ የቅድስት ማርያም ካቴድራልን ህንጻ እያሳየ በሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ብሎ መዘገቡ ብዙዎችን አስቆጥቷል፡፡

ይሄው በቪድዮ ማስረጃ የተያዘው ዘገባ ምሩጽ ባልፈለገውና ከኑዛዜው ውጭ ሆን ተብሎ ለፖለቲካ ፍጆታ ብቻ የተሰራ ሲሆን መንግስት በምሩጽ ሞት ተራ ፖለቲካ ለመጫወት መሯሯጡ እጅግ አሳዛኝና ሳፋሪ ድርጊት ነው ሲሉ አስተያየት ሰጭዎች ተናግረዋል፡፡

የህወሃት አገልጋይ መሆናቸው በቶሮንቶ ህዝብ ዘንድ የሚታወቁ ሰዎች የምሩጽን ሁኔታ በጥብቅ ይከታተሉና አስከሬኑንም ለመውሰድ ብዙ ሙከራዎች ሲደረግ እንደነበር የሚገልጹት የቅርብ ውስጥ አዋቂዎች የጀግናውንና የስደት ህይወቱን ‘ህዝቤ’ን ሲል ያሳለፈውን ምሩጽ ይፍጠር አስከሬን አፈር ሳይለብስ ይፋ ሊወጡ የማይገባቸው በርካታ ክንውኖች ማሳለፋቸውን ለኢትዮጵያ ነገ ገልጸዋል፡፡

ምሩጽ ከትግራይ አካባቢ የተወለደ በዘር ያልተተበተበ ንጹህ ኢትዮጵያዊ ነው የሚሉት እነኝሁ እማኞች ‘ሃግሬ’ንና ‘ህዝቤ’ን ሲል በናፍቆት ህይወቱን ያሳለፈ የቁርጥ ቀን ልጅ ነው ሲሉ መስክረዋል፡፡

ምሩጽ ህዝብ በተጨፈጨፈበት ሰአት ህዝቤን ጨረሱት በማለት ይቆጭ እንደነበርና የህጋዊው ሲኖዶስ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የሆኑትን ቄስ ምሳሌ እንግዳን አስጠርቶ የሽኝት ስነ ስርዓቱ እርሳቸው በሚያስተዳድሩት ቅድስት ማርያም ካቴድራል እንዲሆን ቃል አስገብቶ እንደነበር መዘገባችን አይዘነጋም፡፡

የስምንት ልጆች አባት የነበረው የሻምበል ምሩጽ ይፍጠር አሳክሬን ነገ እሁድ ከንጋቱ 11 ሰአት  አዲስ አበባ ቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ እንደሚደርስ የሚጠበቅ ሲሆን በአቀባበሉም ላይ ታላላቅ አትሌቶችና አድናቂዎቹ እንደሚገኙ ታውቋል።

LEAVE A REPLY