የአድዋን ትርጉም ለሚያቃልሉት የሹምባሽ ልጆችና የቁቤ ዋቆ ትውልድ /መስቀሉ አየለ/

የአድዋን ትርጉም ለሚያቃልሉት የሹምባሽ ልጆችና የቁቤ ዋቆ ትውልድ /መስቀሉ አየለ/

አስራ አራት የአፍሪካ አገሮች ከኮሎኒያልዝም ነጻ ከወጡበት ቀን ጀምሮ እስካሁኗ ሰዓት ድረስ የባርነት ግብር ይከፍላሉ።

ነገሩ እንዲህ ነው፤ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በአስራ ዘጠኝ መቶ አምሳ ስምንት ጊኒ “ከፈረንሳይ ቅኝ ግዛት መውጫው ግዜ አሁን ነው፤ ጊኒ ለጊኒያውያን” ባለች ግዜ ይኽ እርምጃ የፈጠረው ድንጋጤ ባርነት ፍንገላውን ተፈጥሯዊ መብታቸው ላደረጉት ፈረንሳዮች የሚያዋጥ አልነበረም። በመሆኑም ነገሩ ወደኋላ እንደማይመለስ ሲያውቁት በአገሪቱ ውስጥ “አለን” የሚሉትንና ማንቀሳቀስ የቻሉትን ንብረት ሁሉ አግዘው ወደ ፈረንሳይ ካጋዙ በኋላ መንቀሳቀስ የማይችሉትን እንደ ሆስፒታል፣ መጻህፍት፣ ትምህርት ቤቶች፣ መኪኖች፣ ትራክተሮች፣ ትልልቅ ፤ እርሻዎችን ወዘተ በፈንጅ ያጋዩ ሲሆን ከብቶችንና የጋማ ከብቶቹን በሙሉ ደግሞ ለቁጥር ሳያቀሩ ገድለው ወጡ። ይኽ የፈረንሳዮች የበቀል ሰይፍ አላማው ሌላ ተመሳሳይ እርምጃ መውሰድ ለሚፈልጉ የቀሩት የፈረንሳይ ቅኝ ግዛት አገሮች ምንም አይነት የነጻነት ጥቄው ከማንሳታቸው በፊት ሁለት ግዜ ማሰብ እንዳለባቸው ለማጠየቅ መሆኑ ነበር።

ሆኖም ግን በወቅቱ በድፍን አፍሪካ እየተቀታጠለ የመጣው የፓን አፍሪካኒዝምን ወላፈን በቀላሉ የሚጠፋ አለመሆኑ ብቻ ሳይሆን በገዛ አገራቸው ከእንስሳት በታች ቀን ለሚገፉት አፍሪካውያን ከዚያ የተሻለ አማራጭ ግዜ ሊመጣ ስለማይችል ትግሉን አጠናክረው ወደፊት ከመግፋት ውጭ ሌላ አማራጭም አልነበራቸውም።

ነገር ግን ፈረንሳዮች ደግሞ ያንን ሁሉ ጥቅማቸውን አሳልፎ ላለመስጠት እየሄዱበት የነበረው የበቀል ደረጃ አጣብቂኝ ውስጥ የከተታቸው የቶጎ የመጀመሪያው ፕሬዝዳንት ሆነው ስልጣን ላይ የወጡት ሲልቫኖስ ኦሊምፒዮ ለሁለቱም ሃይሎች ግማሽ መንገድ ድረስ የሄደ አንድ አማራጭ የመፍትሔ ሃሳብ አቀረቡ። ይኼውም ፈረንሳዮች አገራቸውን ከሚያወድሙባቸው “በየአመቱ የባርነት ታክስ እንከፍላለን” የሚል ሲሆን ባሪያ ፈንጋዮቹም በውሳኔ ሃሳቡ ተስማምተው “በሰላም” የወጡ ቢሆንም የክፍያው መጠን ግን ውሎ አድሮ ቶጎን ለመሳሰሉ ገና በቅጡ በሁለት እግራቸው ላልቆሙ ትናንሽ አገሮች እንዲህ በቀላሉ የሚገፋ ነገር አልነበረም።

ለዚህም አንዱ ማሳያ በአስራ ዘጠኝ ስልሳ ሶስት ዓም ክፍያው የአገሪቱን አጠቃላይ በጀት አርባ በመቶ ያህል ደርሶ የነበረ በመሆኑ በአገሪቱ ውስጥ ፈጥሮ የነበረው አለመረጋግት ከፍተኛ መሆኑ ነው። ፈረንሳዮች የእጅ አዙር ፍንገላውን የሚያቀላጥፉበት ዋነኛው መንገድ ለነዚህ የቀድሞ ኮሎኒዎች የሚሆን፤ እራሱን የቻለ “ፍራንክ” የሚባልና በፓሪስ ብሔራዊ ባንክ በሚታተም ከረነሲ እንዲጠቀሙ በማድረግ ክፍያውን ደግሞ በወርቅና በመሳሰሉት የሚያወራርዱ ሲሆን ጫናውን መቋቋም የከበዳቸው ፕሬዝዳንት ኦሎምፒዮ ከስምምነቱ በማፈንገጥ የራሳቸውን ብሄራዊ ገንዘብ ማተም ቢጀምሩም በአገሪቱ ውስጥ የሚገኘው የፈረንሳይ ኤምባሲ አንድ ፊደል ላልቆጠረና በአገሪቱ ውስጥ ምን እየተካሄደ እንደሆነ በቅጡ ለማይረዳ ነገር ግን ጠመንጃ መተኮስ የማይሳነው ኢኔቴ ናሲንግቤ የተባለ ቅጥረኛ ነፈሰ ገዳይ ሹምባሽ ስድስት መቶ አምሳሁለት ዶላር በመክፈል አስገደላቸውና ህልማቸውን አጨነገፈው። በቅሎ አመልጣለሁ ብላ ማሰሪያዋን አሳጠረች ነው ነገሩ። ቀጣይዋ ተረኛ ማሊ ነበረች።

የአገሪቱ ፕሬዝዳንት የነበሩት ማዲባ ኬቴ ከስምምነቱ መውጣታቸውን ይፋ ባደረጉ በጥቂት ግዜያት ውስጥ የፈረንሳይ የወታደራዊ አታሸ ባቀናበረው መፈንቅለ መንግስት ተሰልቅጠው በታማኝ ባንዳው ኮሎኔል ሙሳ ትራዎሬ ተተኩ። እንግዲህ አስራ ዘጠኝ ስልሳዎቹ ማለት አፍሪካውያን ከቅኝ ግዛት ቀንበር ወደ ነጻነቱ ጎራ ለመቀላቀል ደፋ ቀና በሚሉበት ሰዓት በአንጻሩ ደግሞ ፈረንሳዮች በያንዳንዱ አገር የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ በመግባት ሁሉንም ነገር ከቁጥጥራቸው ስር እንዳይወጣ ያልተከሉት እንቅፋት ያላፈሰሱት ደም አልነበረም።

በጥር አስራ ዘጠኝ ስልሳ ስድስት የሴንትራል አፍሪካው ዴቪድ ዳኮ በነፍሰ በላው እና በስልጣን ዘመኑ የተቀናቃኝ ፓርቲ አባላቱን መሪዎች እየገደለ ስጋቸውን በማይክሮዌቭ ሳይቀር እየጠበሰ ይበላ እንደነበር በሚነገርለት ቦካሳ በተባለ ታማኝ አሽከራቸው እንዲገለበጥ አደረጉ። ነገሩን አጠናክረው በመቀጠል በሰኔ አስራ ዘጠኝ ስልሳ ስድስት በቡርኪናፋሶ እንዲሁም በአስራ ዘጠኝ ሰባ ሁለት በቤኒን የተፈጸሙት የመፈንቅለ መንግስት ክንዋኔዎች ሁሉ በፈነርሳይ የውጭ ጉዳይ ሚንስቴር መስሪያ ቤት የተመሩ ናቸው። በአጠቃላይ በአለፉት አምሳ አመታት ብቻ በሃያ ስድስት የአፍሪካ አገሮች ውስጥ ስልሳ ሰባት ያህል የመፈንቅለ መንግስት ሲፈጸም ከነዚህ ውስጥ ስልሳ ሁለት በመቶዎቹ የተካሄዱት የቀድሞ የፈንሳይ ቅኝ ግዛት በሆኑት አገሮች ውስጥ መሆኑ በራሱ የሚያሳየው ነገር አለ። ይኽ ማብቂያው የማይታወቅ ውል ቀይ ቢላ ሆኖ አስራ አራት በሚያህሉ የቀድሞ የፈረንሳይ ቅኝ ግዛት ቤተመንስቶች አልጋ ስር ዛሬም ድረስ ተቀምጧል። ወደነዚህ አልጋ የሚጠጋ አፍሪካዊ መሪ ይህንን ስውር ስለት እያወቀ የሚገባ ሲሆን ከዚህች አንድ እርምጃ የሚያፈገፍግ ማንም ቢኖር እጣ ፋንታው የሚያሻማ አይደለም። ባርነት ፍንገላው ዛሬም ድረስ እጁ እንደረዘመ ነው።

LEAVE A REPLY