ከዶ/ር አብይ ንግግር ትኩረት የሳቡ ነጥቦች /ክንፉ አሰፋ/

ከዶ/ር አብይ ንግግር ትኩረት የሳቡ ነጥቦች /ክንፉ አሰፋ/

በዶ/ር አብይ የሹመት ንግግር ውስጥ፤ ይቅርታ፣ እርቅ፣ ካሳ፣ ዲያስፖራ፣ ኤርትራ፣ ሙስና፣ ተቀናቃኝ ሃይሎች፣ የባከነ እድል፣ ስለ ዘረኝነት በሽታ እና የኢትዮጵያ ታላቅነት ተነስተዋል።

“በቅጡ ሳይቧርቁ ሕይወታቸው ለተቀጠፈ ለውጥ ፈላጊ ወጣቶች ለስነ-ልቦናዊ እና አካላዊ ቀውስ ለተዳረጉ ቤተሰቦችና ግለሰቦች ከልብ የመነጨ ይቅርታ እጠይቃለሁ” ሲሉ ጀመሩ ጠቅላይ ምኒስትር አብይ አህመድ።

በተለያየ ግዜያት መስዋዕትነትን ለከፈሉ፤ የመብት ተከራካሪዎች እና የፖለቲካ ስዎች ለደረሰው ጉዳት፣ ለፈሰሰው ደም እና ለጠፋው ህይወት፤ ይቅርታ ብቻ ብለው አላለፉም። ለተፈጠረው ችግር እልባት፤ለተበደለ ወገን ደግሞ ካሳ እንደሚከፍሉም ተናግረዋል። “ከስህተታችን ተምረን ሃገራችንን የምንክስበት ወቅት ነው!” ማለታቸው ራሱ ንግግራቸውን በተግባር ለመተርጎም ያላቸውን ቁርጠኝነት አጉልቶ ያሳየናል። የመርህ እና የእምነት ሰው ናቸውና፣ ይህንን ለማድረግ እንጂ ለማለት ብቻ አልተናገሩትም።

ከየት ጫፍ ተነስተው የት ጫፍ ላይ እንደደረሱ ለተመለከቷቸው ሁሉ፤ ከአንደበታቸው የወጣው ይህ ቃል ምን ያህል በተግባር ሊመነዘር እንደሚችል ይገምታሉ።

ሃገሪቷን ሸብቦ የያዛት የዘረኝነትን በሽታ እናጥፋ ብለዋል። “ማንነታችን የተሳሰረ፣ የተጋመደ እና የተዋሃደ ነው” ይላሉ። ይህችን አባቶቻችን በደማቸው የቆዩዋት ኃያል ሃገር ወደ ቀድሞዋ ታላቅነትዋ እንመልሳት፤ በርካታ ዘመን ተሻጋሪ የሆነ ታሪክ አለን ብለው ሲናገሩ ለሚሰማ ስው እውነትም ይህ ሰው ሊመራኝ ይገባል ማለቱ እንግዳ አይሆንም። ይህ በእኛ ዘመን አልተለመደማ!

ዘላቂ እና ሁሉን አቀፍ ስርዓት ለመገንባት የህዝብ ፍላጎት እና ይሁንታ ያለው መንግስት መመስረት እንደሚገባው በአጽንኦት ተናግረዋል።ተቀናቃኝ ያሉዋቸውን የተቃዋሚ ሃይሎችም ጥሪ አቅርበዋር። ለሃገሪቱ ባይተዋር ሳይሆኑ የለውጡ አካል እንዲሆኑ ጋብዘዋል።

የሰው ልጆች ነጻነት ከመንግስት የሚቸር ስጦታ ሳይሆን የሰው ልጅ በተፈጥሮ ያገኘው ጸጋ እንደሆነ መናገራቸው ስለ ፕሬስ ነጻነት መቆማቸን ይተቁመናል።

ከዲያስፖራ ጋር ያለው የሻከረ ግንኙነት ጠፍቶ ዲያስፖራውም በሂደቱ እንዲሳተፍ ተማጽነዋል። ያለፈውን ምዕራፍ ዘግተን በአዲስ ምዕራፍ እንጓዝ ሲሉ ውጭ ያሉ ኢትዮጵያውያንን በሙሉ ጠርተዋል። ጽንፈኛ ብሎ የሚሳደብ እንጂ፤ ይቅር እንባባል የሚል ልብ የሚነካ ጥሪ ከየትኛውም መሪ አልሰማንም። ፈጣሪ ኢትዮጵያን ይባርክ ብሎ የተናገረ መሪ እስካሁንም አላየንም። ኢትዮጵያ ታፍራና ተከብራ ትኖራለች ብሎስ የተናገረ የኢህአዴግ ሰው መች ተሰምቶ ይታወቃል።

ከኤርትራ መንግስት ጋር ስለሚኖረው እርቅ እና ሰላም እቅድም ጥቅሰዋል። ሁለቱ ሃገር ህዝቦች በደም የተሳሰረ መሆናቸው እና ለክልሉ እድገት ወሳኝ በመሆኑ ለኤርትራ መንግስትም ጥሪ አስተላልፈዋል።

ኢትዮጵያ በርካታ የለውጥ እድል እንደነበራት እና በአመራር ድክመት ሳብያ እነዚህ እድሎችዋን ሳትጠቀም መቅረትዋን ብቻ አልነበረም የተናገሩት፤ እሳቸውን ወደ ጠቅላይ ሚኒስትርነት ያመጣውን ይህንን እድልም ይጠቅሳሉ። የንግግራቸው ቁልፍ ይህ ይመስላል። ይህ እድል እንዳያመልጥ የሚል ይመስላል። ብሄራዊ መግባባትን ፈጥሮ ሁሉን ያቀፈ ፍትሃዊ ስርዓትን መመስረት።

የዶ/ር አብይ ንግግር፣ በመለስ ራዕይ ጀምሮ በመለስ ራዕይ ካበቃው ከኃይለማርያም ደሳለኝ አሰልቺ ንግግር ጋር የሰማይ እና የምድር አይነት ርቀት አለው።

ከኃይለማርያም የተረከቡት ይህ የስልጣን ሽግግር ከጊዜው የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የማህበራዊ ሁኔታዎች ጋር እኩል የሚጓዝና በህዝብ ፍላጎት የሚገዛ፤ ህዝብን አለቃው አድርጎ የሚያገለግል ስርዓት እየገነባን መሆኑን አብስሮናል።
የዶክተር አብይ ንግግር ፓርላማው ለመጥራት እንኳ ይቀፍፈው በነበረው ኢትዮጵያዊነት ጀምሮ በዚያው ነው የጨረሰው። “ኢትዮጵያ የሁላችን ቤት ናት። ልዩነት እርግማን ሳይሆን በረከት ነው” ከሚለው የመቀነስ ሳይሆን የድምር ፖለቲካ እሳቤ – ከሳጥን ውስጥ የወጣ አዲስ እሳቤ ነው።

በርግጥ ይህ የስልጣን ሽግግር ብዙ የተከፈለበት የህዝብ ትግል ውጤት መሆኑ ባይዘነጋም፣ መላው ሕዝብ በእኝህ መሪ ደስተኛ መሆኑ ከፈጣሪ የመጣ ተዓምር ነው ያሰኛል።

አለም በስጋት እና በጉጉት እየጠበቀው ያለው ይህ የለውጥ ሽግግር በተግባር ሲተረጎም ፈተናዎች ሊገጥሙት ይችላል። የሁሉም ድጋፍ ሲታከልበት የተሳካ ለውጥ እንደሚመጣ እርግጥ ነው። የቀድሞው ወዳጃቸው፣ ኸርማን ኮኸን በትዊተር ለዶክተር አብይ በላኩት መልዕክት “አይዞህ ስራህን በድፍረት ስራ ፤ አለም አቀፉ ህብረተሰብ ካንተ ጋር ነው” ብለዋል።

የሹመት ንግግር በተናጋሪው መጻኢ ዘመን ወሳኝ ሚና ይጫወታል። የኦባማ ንግግር በተግባር ባይተረጎምም ብዙዎችን ልብ ገዝቶ ነበር። ፕሬዝዳንት ጆን ኤፍ ኬነዲ በቀዝቃዛው ጦርነት ሰሞን ምዕራብ በርሊን ተሰብስቦ ለነበረ ህዝብ Ich bin ein Berliner በርሊናዊ ነኝ፤ ሲሉ በመናገር የመላ ጀርመንን ልብ ሰልበው እንደነበርም ታሪክ ያወሳል። ይህን ያሉት ኮምኒዝምን ለመምታት እንጂ ለሕዝበኝነት አልነበረም።

የዶ/ር አብይ ንግግር የሕዝብን ልብ ለመግዛት የሚደረግ ቢሆንም ይህ ክፋት የለውም። የማኢያጠግብ እንጀራ ከምጣዱ ያስታውቃል እንዲሉ …በቃሉ የሚኖር ሰው ከአነሳሱ ያስታውቃል። ስልጣን…የማንም ስልጣን ገደል ይግባ! ከሀገር በላይ አይደለም:: ከማናችንም ስልጣናችን፣ ክብራችን፣ ከሀገር በታች ነው!” ብለውን ነበር ኦቦ ለማ መገርሳ።

LEAVE A REPLY