የትግራይ አስተዳደር ፎረም ስብሰባ በእኔ ምልከታ /አስራት አብርሃም/

የትግራይ አስተዳደር ፎረም ስብሰባ በእኔ ምልከታ /አስራት አብርሃም/

ቅዳሜ ዕለት በሀርመኒ ሆቴል የተካሄደው የትግራይ አስተዳደር ፎረም (#Tigray_Governance_Forum) በአኔ እይታ ሁሉም በትግራይ ዙሪያ ያሉ የፖለቲካ አመለካከቶች የተወከሉበትና የተስተናገዱበት በዓይነቱ የመጀመሪያ የሆነ ነው። በእውነቱ አዘጋጀቱ በዚህ ነገር ሊመሰገኑ የሚገባ ነው። ገለልተኛ ለመሆን የሄዱበት መንገድና ያደረጉት ጥንቃቄ እጅግ በጣም ተመችቶኛል።

ለምሳሌ ስብሰባው አንድ ሰው ወይም ድርጅት እስፖንሰር ከሚያደርገው ይልቅ በራሳቸው አዋጥተው ቀሪውን ደግሞ ፍላጎት ያላቸው በመዋጮ መልክ እንዲሸፈን ያደረጉበት መንገድ አስደናቂ ነው። በዚህ ምክንያት ነው፣ ህወሀት ደመኛ ጠላት አድርጋ የምታስበን ሰዎች ሳንቀር ልንገኝ የቻልነው። እንደሚታወቀው ህወሀት የትግራይ ምሁራን ወይ ወጣቶች ብላ ስብሰባ የምትጠራው የራሷን አባላትና ደጋዎች ብቻ ነው።

በስብሰባው ላይ ህወሀት በዶ/ር ደብረፅዮንና በአቶ ጌታቸው ረዳ ተውክሏል። አረናም ሊቀመንበሩ አብርሃ ደስታ፣ ምክትሉ ጎይቶኦም ፀጋይና ሌሎች ወደ አምስት የሚሆኑ አመራሮች ነበሩ። በነገራችን ላይ ከስብሰባው እንደተረዳሁት የዶ/ር አብይ አህመድ ደጋፎዎች፣ የሰልሳይ ወያኔ አመራሮችና አቀንቃኞች፣ የተለያዩ ሲቢል ማህበራት፣ እንደነ ጄራል ፃድቃን ገብረትንሳይ እና ጀነራል አበበ ተክለሃይማት ያሉ የድሮ የህወሀት ታጋዮች፣ ፣ የአግአዚያን አቀንቃኞች ሳይቀሩ በስብሰባው ውስጥ እንደነበሩ ከተነሱት ሀሳቦች መረዳት የሚቻል ነው። እንደዚሁም ለትግራይ ምሁራንና ወጣቶች መከታ እየሆነ ያለው ባለሀብቱ ዳዊት ገብረእግዚአብሄር፣ የብራቬታዛሽን ኤጀንሲ ባለስልጣን የነበረው ኢንጅኔር አሰፋ አብርሃ (የስየ አብርሃ ወንድም)፣ የእርሻ ተመራማሪው ዶ/ር ጉዕሽ፣ ዶ/ር ሙሉ ገብረየሱስና ሌሎችም ሰዎች ተገኝቷል።

በስብሰባው ላይ እነዚህ ነገሮች አስደንቆኛል። አንደኛ አቶ ጌታቸው ረዳ በዚህ ሰዓት ጠላት ማብዛት አንፈልግም ለማለት ያቀረበው ምሳሌ አንደኛው ነው። ቢክቶር ሂጎ የሚባል ፈረንሳዊ ብዙም በእግዚአብሄር መኖር አያምንም ነበር ነገር ግን አርጅቶ ሊሞት ሲል ለማነኛውም አይታወቅም ብሎ ንሰሀ መግባት ፈለገ። አንድ ቄስም ወደ እርሱ አስጠራ፣ ቀሱ መጥተው በእግዚአብሄር መኖር ታምናለህን ይሉታል? ይሉታል፤ አዎ ይላቸዋል። በማርያምስ ታምናህን? ይሉታል፤ አዎ ይላቸዋል። በመጨረሻ ሰይጣንስ ትክዳለህን? ይሉታል። እርሱም “አባታችን በዚህ ሰዓት አዲስ ጠላት የማፈራበት ወቅት ላይ አይደለም ያሉትና እርሱን ተዉት አላቸው” ይባላል። ይህን ተናገሮ ያሳቀን ጌታቸው ረዳ ነው፣ ሌላው የገረመን ነገር የአግዘኢያን እንቅስቀሴ ደጋፊዎች ነን ብለው በድፍረት የተናሩት የአክሱም ዩኒቨርሲቲ መማህራን ናቸው፣ “ህወሀትና አረና መሰረታቸው የካዱ፣ ሸዋዊ መሆን የጣፈጣቸው ድርጅቶች ናቸው” ብሏቸዋል። እኔ ሸዋ ከሚመቻቸው ሰዎች አንዱ በመሆኔ ሀሳቡ ባልደገፍውም፣ ድፍረታቸውን ግን ሳላደንቅ አላልፍም።

በስብሰባው ላይ የተገነዘብኩት ነገር ቢኖር አንደኛ ህወሀት ለዘመናት ያሰፈነችውን ፍርሀት መገርሰሱን ነው፣ ሁለተኛ ደግሞ አዲስ አበባ፣ ወለጋና በሌሎች የኢትዮጵያ አከባቢ ተወልደውና አድገው ትግርኛን እኩል ከትግራይ ከመጣው ሰው ጋር የሚያወሩ የትግራይ ተወላጆች መልከቴ ነው። ይህ አዲሱ ትውልድ ላይ የሚታየው በራስ መተማመን ነገ ሩቅ መንገድ የሚያደርስ ኃይል ነው። ከሁሉም በላይ የደነቀኝ ግን ትግራይ ይህን ያህል ምሁራንና ትንታግ የሆኑ ወጣች ያላት መሆኑ መታዘቤ ነው። ዶ/ር አብይ አህመድ እንዳለው በአሁኑ ኢትዮጵያ አገራችን ካሏት ምሁራንና ትንታግ ወጣቶች ላይ እነዚህን በመደመር የተሻለ አገርና ህዝብ መፍጠር እንደሚቻል ነው። በስብሰባው ላይ ጄኔራል አበበ ተክለሃይማት የሰጡትን ማሳሰቢያ ያህል ያረካኝ ነገር የለም።

ጄኔራሉ እንዲህ ነው ያሉት፦ “እነዚህ መቀሌ ከትመው ያሉት የህወሀት ሽማግሌዎች አትስማቸው፣ እነርሱ ናቸው ከስልጣን የወረዱት እንጂ የትግራይ ህዝብ አይደለም፣ የትግራይ ህዝብ መስዋዕትነት አይደለም ያሳሰባቸው፣ የትግራይ ህዝብ ችግር አይደለም ያንገበገባቸው፣ እነርሱ ያሉት ለምን እኛ ከስልጣን እንድንለቅ ተደረገ፣ ለምን ክብር አልተሰጠንም ነው ይህ ነው እያሉ ያሉት በዚህ ምክንያትም የትግራይ ህዝብ ቁጣና ንዴት ውስጥ እንዲገባ በማድረግ ነው ህዝቡን ማነሳሳት እየፈለጉ ይህ ደግሞ የትግራይ ህዝብ አጀንዳ አይደለም፣ ስለዚህ ይህ ጉዳይ የእርነርሱ እንጂ የህዝብ ጉዳይ እዳልሆነ ተረድተን መጠንቀቅ ነው ያለብን”።

እኔም የምለው ይህንኑ ነው፣ የትግራይ ህዝብ ዘላቂ ጥቅሙን ነው ማሰብና ማራመድ ያለበት እንጂ የህወሀት መሪዎች Hostage ሆኖ መቀጠልና መጠቀሚያ መሆን የለበትም። የቅርብ አደጋዎቻችንና ስጋቶቻችን በመለየት እንደአገርም እንደክልልም ማድረግ የሚኖርብን ጥንቃቄዎች መለየትና መዘጋጀት እንጂ ወደ መቃብር እየተንደረደሩ ካሉት የህወሀት መሪዎች ጋር አብረን ወደ መቀመቅ መውረድ የለብንም። ከተደቀምንበት ብዙ አገራዊና ክልላዊ አቅም አለ፣ ሁሉም በተደራጀና በተጠና መልኩ ማንቀሳቀስ ያስፈልጋል። ይህ አገር የብሄር ብሄረሰቦች አገር ነው፣ ማንም የበላይና የበታች የሚሆንበት እድል የለም፣ ከኢትዮጵያዊነትም ሊገፋን የሚችል ኃይል አይኖርም።

ጥቅማችንና የአንድነታችን አስጠብቀን፣ ተከብረን መኖር የምንችልበት ዘመን ነው እየመጣ ያለው፣ ከዘመኑ ጋር ከማዕበሉ ጋር ለመዝለል ነው መዘጋጀት ያለብን።

LEAVE A REPLY