የትግራይ ክልል ኩርፊያ | ፈቃዱ ዘ ኃይሉ

የትግራይ ክልል ኩርፊያ | ፈቃዱ ዘ ኃይሉ

የትግራይ ክልል ፌዴራሊዝሙ ከመመሥረቱ በፊት ጀምሮ በሕወሓት ሲመራ የኖረ ክልል ነው። ሕወሓት በተለይ በትጥቅ ትግሉ ወቅት ከትግራይ ሕዝብ ከፍተኛ ድጋፍ የነበረው ቡድን ሲሆን፥ ቀሪዎቹን የኢሕአዴግ አባል ድርጅቶችም በአምሳሉ የሠራቸው መሆኑ የአደባባይ ምሥጢር ነው።

የትግራይ ክልል ፌዴራሊዝሙ ከመመሥረቱ በፊት ጀምሮ በሕወሓት ሲመራ የኖረ ክልል ነው። ሕወሓት በተለይ በትጥቅ ትግሉ ወቅት ከትግራይ ሕዝብ ከፍተኛ ድጋፍ የነበረው ቡድን ሲሆን፥ ቀሪዎቹን የኢሕአዴግ አባል ድርጅቶችም በአምሳሉ የሠራቸው መሆኑ የአደባባይ ምሥጢር ነው። አሁን በኢትዮጵያ የሚታየው ለውጥ “መፈንቅለ ሕወሓት” ቢባል አያንስበትም፤ ለዚህም ይመስላል ከፍተኛ ተግዳሮት እየገጠመው ያለው ከሕወሓት የሆነው። በገዛ የእጅ ሥራዎቹ የታመፀበት ሕወሓት የሚያስተዳድረውን ትግራይ ክልል የኩርፊያ መግለጫ አድርጎታል።

“ትግራይ ተከባለች”

አንጋፋዎቹ የሕወሓት ታጋዮች እና ታዋቂዎቹ የሕወሓት ደጋፊዎች መቐለ ከተማ ገብተው ማዕከላዊ መንግሥቱ ላይ ያላቸውን ተቃውሞ ከዚያው እያራመዱ ይገኛሉ። ከተቃውሟቸው ዋነኛው አቤቱታ “ትግራይ ተከባለች” የሚለው ነው። የትግራይ ክልል እና አማራ ክልሎች የገቡበት እሰጥ አገባ አንዱ ምሳሌያቸው ነው። በፊት የተቃዋሚዎች አጀንዳ የሆነው “የወልቃይት እና የራያ ጥያቄ” አሁን የአማራ ክልልም የተቀበለው ይመስላል። በዚህም የጦርነት ክተት አዋጅ የሚመስል ፕሮፓጋንዳ በሁለቱም ወገን ሲራገብ ነበር። የጦርነት ፕሮፓጋንዳው የሃይማኖት አባቶች የሁለቱን ክልሎች ርዕሰ ብሔሮች እስከሚያሸማግሉ ድረስ ጮሆ የሚሰማ ነበር። በዚህም ሳቢያ ከመሐል አገር ወደ ትግራይ የሚሔዱት መንገዶች መቼ በተቃውሞ እንደሚዘጉ እና መቼ እንደሚከፈቱ እንኳን ማወቅ አልተቻለም፤ በትግራይ ለሸቀጦች ዋጋ መናርም መንሥኤ ሆኗል።

በሌላ በኩል በኢትዮጵያ እና ኤርትራ መሐል የወረደው ዕርቀ ሰላም የዚሁ ትግራይን የመክበብ አካል እንደሆነ የትግራይ ፖለቲከኞች እየገለጹ ነው። የኤርትራው መሪ ኢሳያስ አፈወርቂ ሕወሓት ላይ የከፋ ትችት እየሰነዘሩ መሆናቸው እና የሕወሓት አመራሮች በዕርቀ ሠላሙ ሒደት የፈለጉትን ያህል ባለመሳተፋቸው ምክንያት የፌዴራሉ መንግሥት ከኤርትራ መንግሥት ጋር ያበረባቸው ያክል ተሰምቷቸዋል። የሕወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል የሆኑት ጌታቸው ረዳ፣ ኢሳያስ አፈወርቂ አማራ ክልል ጉብኝት ላይ በነበሩበት ወቅት “ወደ ትግራይ ቢመጡ የተሻለ በቋንቋ መግባባት ይችሉ ነበር” ብለው ለሚዲያ መናገራቸው ቅናት ተደርጎ ተወስዶባቸዋል።

ከዚህም በላይ ዕርቀ ሠላም በመውረዱ ምክንያት የሰሜኑን ዕዝ ሊያግዝ ትግራይ ሰፍሮ የነበረው ማዕከላዊው ዕዝ የመከላከያ ሠራዊት ክፍል ወደ መሐል አገር ሲንቀሳቀስ በዚህ “ትግራይ ተከባለች፣ ልንጠቃ ነው” ፕሮፓጋንዳ የተነሳሳው ሕዝብ መንገድ ዘግቶ ሠራዊቱን አላሳልፍም እስከማለት ደርሷል። (ተቃዋሚዎቹን ባለመታገስ የሚታወቀው የትግራይ መንግሥትም ወጣቶቹን ባለማስቆሙ፣ ምንም እንኳን የኋላ ኋላ ለማስተባበል ቢሞክርም ሕወሓት ራሱ ያስተባበረው የመንገድ መዝጋት እንደሆነ ተገምቷል።)

በተመሳሳይ፣ በታኅሣሥ ወር 2011 የሱዳኑ መሪ ከኢትዮጵያ መሪ ጋር ጅማ ላይ በተገናኙበት ወቅት ላይ ባደረጉበት ወቅት፣ በትግራይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይን ለመቃወም በርካታ ሰልፎች እየተካሔዱ ነበር። ሰልፈኞቹ ከያዙት መፈክር መካከል “አልበሽር እናመሰግናለን” የሚል ይገኝበታል። አልበሽር እና ኢሳያስ ከፌዳራሉ መንግሥት ጋር ያላቸውን ግንኙነትነት በአንድ በኩል በቅናት፣ በሌላ በኩል በማባበል ለመሳብ የሚሞክሩት የትግራይ መሪዎች ሕዝባቸውን ተከበናል እያሉ ከሚያሳምኑበት ጉዳይ ውስጥ እነዚህ የውጭ ግንኙነቶች ይገኙበታል።

ትግራይ እና ሕወሓት
ሕወሓት ማዕከላዊው መንግሥት ላይ ከፍተኛ ተሳትፎ የነበረውን የትግራይ ሕዝብ ወደ ዳር (periphery) እንዲገፋ ምክንያት ሆኗል። ሆኖም በዚህ ራሱ ተወቃሽ ሊሆን በሚገባበት ጉዳይም ድጋፍ መሰብሰቡን አላቆመም። “በትግራይ ሕዝብ እና በሕወሓት መካከል ልዩነት የለም” የሚል አቋም የሚያራምደው ሕወሓት፥ በፖለቲካ ጫወታ ሲሸነፍ ሕወሓት ላይ የተወሰደውን እርምጃ በሙሉ የትግራይ ሕዝብ ላይ የተወሰደ እርምጃ ነው እያለ ይናገራል። በዚህም ምክንያት ከአዲሱ አመራር መምጣት በፊት ሕወሓት ላይ ምሬት የነበረው ብዙኃን ትግራዋይ፥ አሁን ክልሉን በመከላከል ሥም የሕወሓት ደጋፊ ወደ መሆን እየተሸጋገረ እንደሆነ እየተነገረ ነው።

ለዚህም በትግራይ ክልል የሚካሔዱት የፌዴራል መንግሥቱን የሚቃወሙ ሰልፎች ማሳያ ናቸው። ሌላው ቀርቶ የሑመራ ድንበር በተከፈተበት የገና ዕለት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድን “ሌባ ሌባ” እያሉ ይሰድቡ የነበሩ የአካባቢው ነዋሪዎች ይህንን የትግራይ ማኩረፍ የሚያሳዩ ምልክት ናቸው።

ከድጡ ወደ ማጡ

የፖለቲካ ኩርፊያው እና እሰጥ አገባው እስከ ባለፈው ሳምንት ድረስ በመግለጫዎች እና በቴሌቪዥን ፕሮፓጋንዳዎች ብቻ ነበር የሚስተዋለው። ባለፈው ሳምንት፣ የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ ምክር ቤት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአዋጅ ያቋቋመውን የማንነት እና አከላለል ጥያቄዎች አጣሪ ኮሚሽን በመቃወም አቋም ሲወስድ፥ ኩርፊያው ኦፊሴላዊ ዕውቅና አግኝቷል።

በመሠረቱ፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በድምፅ ብልጫ የሚወስነውን ውሳኔ “እኔን ካልተስማማኝ” ብሎ የመሻር መብት አንድም ኢ-ዴሞክራሲያዊ ነው፣ በሌላ በኩል ደግሞ ለክልሎች አልተሰጠም። ይሁንና አሁን የትግራይ ክልል አቋም አዋጁን በክልሉ ተፈፃሚ እንዳይሆን እስከማድረግ ድረስ ይዘልቃል።

የትግራይ ክልል ኩርፊያ የኢትዮጵያን ኅልውና አደጋ ላይ ከሚጥሉ ፈተናዎች አንዱ ነው። ይሁን እንጂ የኩርፊያው አንድ አካል የሆነው የፌዴራል መንግሥትም የሚገባውን ትኩረት የሰጠው አይመስልም። አብዛኛው የኢትዮጵያ ክፍል አንፃራዊ የለውጥ ንፋስ እየተነፈሰ ባለበት ወቅት፥ የትግራይ ሕዝብ ግን የተለየ የጭቆና ደሴት ውስጥ ሆኖ ቀጥሏል።

በዚህ መካረር መሐል ቀጣዩን ምርጫ በትግራይ እንዴት ማካሔድ ይቻላል? ሕወሓትስ ከኢሕአዴግ ጋር አብሮ የሚሠራው (ወይም አብሮ ሳይሠራ አብሮ የሚኖረው) እስከመቼ ነው? የሚሉት ጥያቄዎች ገና ብዙ ትርምስ እንደሚኖር አመላካቾች ናቸው።

LEAVE A REPLY