የዘር መንግሥት አገር ያተራምሳል | ታፈሰ በለጠ

የዘር መንግሥት አገር ያተራምሳል | ታፈሰ በለጠ

በአሁኑ የኢትዮጵያ ሁኔታ የክልል፣ የዘር፣ የጎሣ፣ የጎጥና የቋንቋ ሥነ መንግሥታዊ ቡድኖች አሉ፡፡  በዜግነት ላይ የተመሠረተና አገር-አቀፍ ቡድን ካልተጠናከረ አንድ ቡድን ብቻውን አገሪቱን ማስተዳደር አይችልም፡፡ ምንጊዜም አናሳ ሆኖ ነው የሚገኘው፡፡ ወያኔ ብቻውን ኢትዮጵያን ማስተዳደር ስላልቻለ የአማራን እንዲሁም የኦሮሞና የደቡብ «ብሔሮችን» አጣምሮ በበላይነት ለሀያ ሰባት ዓመታት «ክርን አማስት» እያለ ቆየ፡፡ አሁን ግን ከወያኔ በስተቀር ሌሎቹ ክርስትና እየተነሱ «..ዴፓ» ተሰኝተዋል፡፡ ወያኔ አሁንም ነጻ አውጪ ግንባርና ጠመንጃ ያልፈታ ነው፡፡

የሥነ መንግሥት (የፖለቲካ) ተወዳዳሪ ቡድኖች በዘር፣ በጎሣ፣ በአካባቢ ስምና በሃይማኖት ከተሰየሙና ከተንቀሳቀሱ አባሎቻቸውም ሆኑ ደጋፊዎቻቸው የየራሳቸው ሰዎች ይሆናሉ፡፡ ሁሉም ሁለንተናዊ ራዕይ አይኖራቸውም፡፡ የአማራ ሥነ መንግሥት ቡድን አባልነት ካልተስማማኝ ወደ ኦሮሞው ለመቀላቀል እንዴት እችላለሁ፤ ኦሮሞ መሆን አለብኝ፡፡ መርሆዉና ዓላማው በራሱ አቀፍ መልካም ቢመስልም በአባልነት ተቀባይነት አይኖረኝም፡፡ የትግራይ የነÍነት ግንባር አባልም መሆን አልችልም፡፡ ከትግራይ ሰው በስተቀር የሌላ አካባቢ ሰው አባል ነው ሲባል አልሰማሁም፡፡

መንግሥት ለመምራት የሚመኙ ቡድኖች በአገራዊ ስፋት ላይ ማተኮር አለባቸው፡፡ በአገር እርከንና ደረጃ ላይ የተንደረደረ ጽንሰ-አሳብ መቅረጽ ያስፈልጋል፡፡ የአንድ የሥነ መንግሥት ቡድን የሚቀርጸው ንድፍና መርሆ የመንግሥትነት አስተዳደር ቅድመ ሁኔታና ራዕይ ሁሉንና አገር አቀፍ መሆን አላበት፡፡ አንዱ ቡድን ከሌላው የሚለየው በምጥቀተ-አሳቡና በአገራዊነቱ ስለሆነ ለአባል ምልመላው የምርጫ ጉጉት ዝንባሌን በአምራቂነት መማረክ አለበት፡፡ የጠበበ የመመረጫ ፍኖተ-ሰነድም አገር-አቀፍነት ድባብና ሚና ካልተላበሰ ምንጊዜም በአገር መንግሥትነት በንጸህ መመረጥና መሠየም ያዳግተዋል፤ የምርጫ ኮሮጆ ካልሰረቀ በስተቀር፡፡

የኢትዮጵያ በዘር፥ በጎሣ፥ ባካባቢ ስም በሥነ-መንግሥት ቡድንነት መዋቀር መወገዝና በሕግ መከልከል አለበት፡፡ ይህንን ለማድረግ ድፈረትና ህሊናዊ ዘይቤ ይጠይቃል፡፡ የዘር ጉዳይ አያዋጣም፥ ያደድባል፥ ያደነቁራልም፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ዜጎች ሁሉም በእኩልነት መሳተፍ አለባቸው፡፡ እስካሁን የአንድ ብሔር የቡድን መብት ከሌላው ብሔር መብት አይመሳሰልም፡፡ እንዲያውም መብት የሌለው አብላጭ ይመስለኛል፡፡ በአሁኑ ጊዜ አንዱ ከሌላው የበለጠ እኩል ነው፡፡ ምርጫ በዜግነት ላይ ከተመሰረተ አንድ ዓይነት መብትና ግዴታ ይኖራል፡፡ መብትና ግዴታ ላንዱ በማንኪያ ለሌላው በጭልፋ አይለካም፡፡ መልክዐ-ምድርም ሆነ ቆላ ደጋ አበላላጭ መብት አይፈጥርም፡፡

በዘርና በጎሣ የሥነ-መንግሥት ቡድን ወይም ድርጅት ማራመድ በኢትዮጵያ ብቻ ነው የተከሰተው፡፡ በየትም አገር የለም፡፡ በሁሉም አገሮች በርእዮተ-ዓለም፣ በምጥቀተ-አሳብና በአገር የመምራት መርሆ ላይ የተመሠረተ ነው እንጂ የተወሰኑ የአገሪቱ አካባቢ ሰዎችን የሚወክል መሆን የለበትም፡፡ የዘር፣ የጎሣ ወይም የቋንቋ የድርጅት እንቅስቃሴ ተጣምሮም ቢሆን አገር በሠላም ካለመምራትም አልፎ የማይከለስ፣ የማይቀነስ፣ የማይጨመርና ራዕይ የሌለው መካን አሳብ ነው፡፡

ሁለት አገሮችን ልጥቀስ፤ ጋና እና ኬንያ፡፡ በጋና ሕገ-መንግሥቱን መሠረት በማድረግ በ1992 (ኢ.አ.) ስለ ሥነ-መንግሥታዊ ቡድኖች አመሠራረት በዝርዝር ባወጣው ሕግ ቁጥር 281 እና አዋጅ ቁጥር 574 (3.1) የሚከተለውን ይደነግጋል፥

« ማንም የሥነ-መንግሥት ቡድን በዘር፣ በአካባቢ (ክልል)፣ በሙያ፣ ወይም ሃይማኖትን መሠረት በማድረግ፤ በተለይም የዘር፣ የጎሣ፣ የክልል፣ የሙያ ወይም ሃይማኖታዊ ልዩነቶችን የሚያነሳሱ ቃላቶችን፣ መፈክሮችን ወይም ምልክቶችን የሚያቀነቅኑ ይከለከላሉ››

በተመሳሳይ የኬንያ ሕገ-መንግሥት (2002 ኢ.አ.) ክፍል 3 ቁጥር 91 (2) በሃይማኖት፣የቋንቋ፣ በዘር፣ በብሔር፣ በጸታ ወይም በክልል ወይም በጥላቻ ላይ የተቋቋሙ የሥነ-መንግሥት ቡድኖችንና ተመሳሳይ ድርጅቶችን በመንግሥት ምሪት የምርጫ ውድድር እንዳይሳተፉም እንዳይኖሩም ያግዳል፡፡

አገር-አቀፍነት ባሕሪ የተላበሱና ስለ አገር አንድነትና ሰላም የሚያራምዱትን ቡድኖች የኬንያ ሕገ-መንግሥት ይደግፋል፡፡ በሁለቱም አገራት ሕጎቹ ከተደነገጉ ጀምሮ ሰላምና እድገት እየጎላ ነው፡፡ በተለይ በጋና ሰላማዊ የመንግሥት የምርጫ የሥልጣን እርክክብ በየጊዜው በሰላም ሲከናወን እየመሰከርን ነው፡፡

ነሐሴ 15 ቀን 1987 የታወጀው ኢትዮጵያው ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 38 የመምረጥና የመመረጥ መብት ይለግሳል እንጂ ማብራሪያ አይሰጥም፡፡ ‹‹ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ዜጋ በቀለም፣ በዘር፣ በብሔር፣ በብሔረሰብ፣ በጸታ፣ የቋንቋ፣ በሃይማኖት በፖለቲካ ወይም በሌላ አመለካከት ወይም በሌላ አቁዋም ላይ የተመሠረተ ልዩነት ሰይደረግበት በቀጥታና በነጻነት በመረጣቸው ተወካዮች አማካኝነት በሕዝብ ጉዳይ አስተዳደር የመሳተፍ መብቶች አሉት›› ይላል እንጂ ተመራጮቹ በምን ላይ በተመሠረተ የድርጅት መርሆ ተመረጡ ብሎ አይገልጥም፡፡ ‹‹በቀጥታና በነጻነት በመረጣቸው ተወካዮች›› መሠረቱ ምንድነው?

ሌላው ደግሞ አንቀጽ 56 ‹‹የፖለቲካ ሥልጣን በምክር ቤቱ አብላጫ መቀመጫ ያገኘ የፖለቲካ ድርጅት ወይም ጣምራ ድርጅቶች የፌደራሉን መንግሥት በሕግ አስፈ .   ሚነት አካል ያደራጃል-ያደራጃሉ ይመራል-ይመራሉ›› ይላል፡፡ የሥነ-መንግሥት ድርጅት መቋቋም ይዘት ፍንጭ አይሰጥም ወይም ከሕገ-መንግሥቱ የሚፈልቅ ሕግ እንደሚወጣ አያመለክትም፡፡ ሆኖም በሕገ-መንግሥት ደረጃ አገራዊነት የሌላቸው ድርጅቶች እንዳይኖሩ መከልከል ነበረበት፡፡

ይህም ካልሆነ በአሁኑ ሰዓት ምክር ቤቱ ለዘላቁ ሰላም ሲል በአዋጅ ወይም በመንጪ ሕግ መልክ በመደንገግ መንግሥት የመምራት ስልጣን ፈላጊ ድርጅቶች በዘር፣ በብሔር፣ በቋንቋ፣ በሃይማኖትና በክልል እንዳይደራጁ፣ የተደራጁም ቢኖሩ መመሪያቸው በዜግነትና በኢትዮጵያዊነት ላይ እንዲያተኩር ቢያደርጉ፡፡ የድርጅቶቹ የሀላፊነት የውስጥ ምርጫ ሥነሥርዓትም በአዋጅ መወሰን ይኖርበታል፡፡

ሰላማዊ ሥርዓተ-መንግሥት በኢትዮጵያ እንዲዘረጋና ዘላቂ እንዲሆን በዘር ላይ የተመሠረቱና የሚመሠረቱ ቡድኖች አገራዊነት ባሕሪ እንዲይዙ በሕግ መደንገግ አለበት፡፡ በአገር አቀፍነት የሚደራጅ ቡድን በመላ የአገሪቱ ክፍሎች የምርጫ ውድድር ዘመቻ ማከናወን ይችላል፡፡

LEAVE A REPLY